“የመከላከያ ሰራዊት እና የህወሓት ታጣቂዎች በአንዳንድ ቦታዎች በአካል ተገናኝተው ሀሳብ እየተለዋወጡ ነው”፦ ጄኔራል ታደሰ ወረደ

0
1210

ማክሰኞ ኀዳር 13 ቀን 2015 (አዲስ ማለዳ) የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እና የትግራይ ታጣቂ ኃይሎች በአንዳንድ ቦታዎች በአካል ተገናኝተው ሀሳብ እየተለዋወጡ መሆኑን የህወሓት ታጣቂዎች ዋና አዛዥ ጄኔራል ታደሰ ወረደ ገለጹ።

አዛዡ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ “የተደረሰው የሰላም ስምምነት ሂደት ረጅም ርቀት እንደሚወስድ አምናለሁ” ብለዋል።

የሰላም ስምምነት በኹለቱም ሃይሎች ፍላጎት ላይ የተመሰረተ መሆኑን የገለጹት ጄኔራል ታደሰ፤ ለተግባራዊነቱ በቁርጠኝነት መስራት እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል።

ነገር ግን የአማራ ታጣቂ ሃይሎች እና የኤርትራ ጦር በተለያዩ አካባቢዎች በትግራይ ተወላጆች ላይ ከፍተኛ ግፍ እየፈጸሙ መሆኑን በመግለጽ፤ ይህንንም ለማስቆም የኢትዮጵያ መንግስት ኃላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባም ማሳሰባቸውን ድምጸ ወያኔ ዘግቧል።

ከትጥቅ ማስፈታት ጋር በተያያዘም ለቀረበላቸው ጥያቄም “ይህ የትግራይ ህዝብ ደህንነት በዘላቂነት በሚረጋገጥ እንጂ አደጋ ላይ በሚጥል መልኩ በፍፁም እንደማይሆን” ተናግረዋል።

የኹለቱን አካላት ግንኙነት አስመልክቶ በኢትዮጵያ መንግስት በኩል እስከአሁን የተባለ ነገር የለም።

መልስ አስቀምጡ

Please enter your comment!
Please enter your name here