የሳይበር ደኅንነት ወር መከበር መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት የሳይበር ደኅንነት ተጋላጭነታቸውን እንዲለዩና እንዲቀንሱ ለማድረግ ጉልህ ፋይዳ እንዳለው የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር መግለጹ ተዘግቧል።
የሣይበር ደኅንነት ወሳኝ መሆኑ የተገለጸው ከጥቅምት 1 እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2015 ሲካሄድ በነበረው 3ኛው ሀገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር ማጠቃለያ ዙሪያ በተሰጠው መግለጫ ነው ተብሏል።
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ባለፈው አንድ ወር ሲያካሂድ በቆየው የሳይበር ወር የተከናወኑ ተግባራት በተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ሰለሞን ሶካ ማብራሪያ እንደተሰጠ የተጠቀሰ ሲሆን፤ ወሩ የሳይበር ደህንነትን ተጋላጭነትን መቀነስ፤ በሳይበር ዘርፍ የተሰማሩ አካላት ሚናቸው እንዲጨምር ማድረግ፤ በዘርፉ የሚታየውን የሰው ሀብት ውስንነት ማጠናከር ብሎም ማህበረሰብ አቀፍ ንቃተ ህሊናን የመጨመር አላማዎችን ይዞ መከበሩን የተለያዩ ሚዲያዎች ዘግበዋል።
የግሉን ዘርፍ ከተለያዩ የመንግስት ተቋማትና ባለድርሻ አካላት ጋር እንዲገናኑ ምቹ ሁኔታ የፈጠረ ወር እንደነበርም ሰለሞን ተናግረዋል ተብሏል።
የሳይበር ወር በወርሃ ጥቅምት የሳይበር ደህንነት ማስጨበጫ የንቅናቄ መርሐ ግብር ሲሆን፣ ወሩ በኢትዮጵያ ለሦስተኛ ጊዜ በዓለም አቀፍ ደረጃ ደግሞ ለ19ኛ ጊዜ ነው የተከበረው።
ቅጽ 5 ቁጥር 210 ኅዳር 3 2015