ፈተናው ተሰርቋል እንዲሁም ሌሎች ምክንያቶችን በማንሳት አንፈተንም ያሉ ከ12 ሺሕ በላይ ተማሪዎችን ትምህርት ሚኒስቴር በድጋሚ እንዲፈትን እናት ፓርቲ ጠይቋል።
እናት ፓርቲ ለመገናኛ ብዙኀን በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ ትምህርት ሚኒስቴር በፈተና አሰጣጥ ዙሪያ ያመጣውን ለውጥ እናደንቃለን ያለ ሲሆን፣ ያልተፈተኑ ተማሪዎችን በተመለከተ ያስተላለፈውን ውሳኔ ግን እንዲያጤነው ሲል ጠይቋል።
ፓርቲው በአማራ ክልል የሚገኙና ፈተናውን አንወስድም ያሉ ከ12 ሺሕ በላይ ተማሪዎች ለጥፋታቸው ኃላፊነት መውሰድ ያለባቸው ቢሆንም፣ ክልሉ በአጠቃላይ ከቆየበት ሁኔታ፣ ተማሪዎቹ ያሉበት እድሜና መሰል ውዥንብሮች ተጽዕኖ አድርገውባቸው በመሆኑና በጥቂቶች ጥፋት አብዛኞቹ ሰለባ መሆናቸውን እናምናለን ብሏል።
ሚኒስቴሩ በአንድ በኩል የሠራውን ሥራ ጥላሸት የቀባ ውሳኔ ወስኗል ያለው ፓርቲው፣ ከመንግሥት ጠባይ የማይጠበቀውን እልህ መጋባት ትቶ በቀጣይ የፈተና ጊዜያትና ዓመታት ለሚፈተኑ ተማሪዎች ጭምር ጥብቅ መልዕክት በሚያስተላልፍ መልኩ ተመጣጣኝ ቅጣት በማሳለፍ ድጋሚ ሊፈተኑ የሚችሉበትን እድል እንዲያመቻች በአጽንኦት ጠይቋል።
ቅጽ 4 ቁጥር 208 ጥቅምት 19 2015