ዕረቡ ግንቦት 17 ቀን 2014 (አዲስ ማለዳ) በኢትዮጵያ የፀጥታና ደህንነት ኦፕሬሽን አካሄድን በተመለከተ ግምገማ እየተካሄደ ነው፡፡
የፀጥታና ደህንነት ኦፕሬሽን አካሄድ ግምገማ ላይ የጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ እና ምክትል ኢታማዦር ሹም ጀነራል አበባው ታደሰ እንዲሁም የክልልና የመከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
የብሄራዊ ደህንነት ምክር ቤት በወሰነው መሰረት በኢትዮጵያ የህግ የበላይነትን በማስከበር የህዝብ ደህንነት ስጋትን ማስወገድ፣ ለውጭ ጠላት ምቹ ሁኔታን እየፈጠረ ያለውን የውስጥ ተጋላጭነትን መቀነስ፣ እንዲሁም ሰላምን በማስፈን ልማትን ማረጋገጥን ታሳቢ ተደርጎ ወደ ሥራ መገባቱ ይታወሳል።
ምክር ቤቱ የተለያዩ የፖለቲካ ፍላጎት ያላቸው የታጠቁ ሀይሎችን በመለየት መልክ ማስያዝ፣ ታጥቀውና ተደራጅተው በህገወጥ መንገድ የተሰማሩ ፅንፈኛ ቡድኖችን ወደ ህጋዊ ሥርዓት እንዲገቡ ማስቻልን ታሳቢ ያደረገ አቅጣጫ ማስቀመጡ ተነግሯል።
በዚህም የፀጥታ አካላት እንዲሁም የክልል አመራሮች የፀጥታና ደህንነትን በማረጋገጡ ሂደት የተሰሩ ሥራዎች ተገምግመው ቀጣይ አቅጣጫ የሚቀመጥ ይሆናል መባሉን ኢቢሲ ዘግቧል፡፡