በአዲስ አበባ እና በኦሮሚያ መካከል ያለው የአስተዳደር የወሰን ጉዳይ አልባት እስከሚያገኝ የኦሮሚያ ክልልን ጥያቄ እያነሳባቸው ያሉ የክልሉን ወሰን አልፈው የተገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ለተጠቃሚዎች በዕጣ ማስተላለፍ ትክክል እንዳልሆነ የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ተቃውሞውን አሰማ።
በመሆኑም ይህ ውሳኔ ሥራ ላይ እንዳይውል የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ጠንካራ አቋም መያዙን የክልሉ መንግሥት ካወጣው መግለጫ ለማወቅ ተችሏል። ይህ አቋም በቀዳሚነት የሕዝቡን ተጠቃሚነት በማስጠበቅ የመነጨ እንጂ የአገሪቱን ብሔር ብሔረሰቦች አብሮ የመኖር እሴት ከመጥላት የመነጨ አለመሆኑ ከግንዛቤ ሊገባ ይገባል ሲል ክልላዊ መንግሥቱ በመግለጫው አትቷል።
በጉዳዩ ላይ የአዲስ አበባን አቋም ለማወቅ አዲስ ማለዳ የከንቲባ ጽሕፈት ቤት የሥራ ኃላፊዎችን በተደጋጋሚ ብትጠይቅም መረጃ ለመስጥ አልፈቀዱም፡፡
ቅጽ 1 ቁጥር 17 የካቲት 30 ቀን 2011